Get Mystery Box with random crypto!

የኢትዮጵያ አዕማድ-ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ!     በዐዲስ አገር አላሚዎች የገጠማት ፈተና ምንድነው? | Tadele Tibebu - ታደለ ጥበቡ

የኢትዮጵያ አዕማድ-ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ!

    በዐዲስ አገር አላሚዎች የገጠማት ፈተና ምንድነው?...

(በሙሉዓለም ገ/መድህን)
***
ስለ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ-ክስቲያን የታሪክ ሊቃውንት መዛግብት አጣቅሰው እንደሚያስተምሩት፣ ክርስትናን የተቀበለችው በመጀመሪያው ምዕተ-ዐመት ይሁን እንጂ፤ በሲኖዶስ ሕግ የኤጲስ-ቆጶስ መንበር የተሰጣት በአራተኛው ምዕተ-ዐመት ነው፡፡ በ350 ዓ.ም. ደግሞ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ሃይማኖት ሆኖ ከተተከለ በኋላ፣ እስከ 1966 ዓ.ም. ቆይቷል፡፡

ሀገረ-መንግሥቱን በማበጀቱ ሂደት የነበራት አበርክቶም የትየሌለ ነው። በአልቦ-መንግሥታዊ ተቋማቱ ዘመንም፣ እልፍ-አእለፍ የሕዝብ አስተዳዳሪዎችን አብቅታለች። የዳኝነት ሥራውንም ያሳለጡ ፍርድ አዋቂዎች አፍርታለች። ተጽዕኖዋ በበዛበት በዛ ገናና ዘመኗም፣ ከአገራቸው ተገፍተው የተሰደዱ የእስልምና ሃይማኖት ተከታዮችን፣ ከእነ ዐዲሱ አስተምህሮቻቸው ከተወነጨፈባቸው ቀስት ከለላ ሆናለች። ይህ እንግዲህ የዴሞክራሲ ስሙ እንኳ በማይታወቅበትና ባህላዊ ሥልጣኔ በነገሠበት ድሮ መሆኑ፣ ለማመን ቢቸግርህ አይደንቅም።

ቤተ-ክርስቲያን በእነዚህ ዘመናት ሁሉ የኢትዮጵያ አዕማድ በመሆን ግዙፍ ማኀበራዊ ተቋምነቷን ያስመሰከረች አምሳለ-ሀገር ነች፡፡

በተለይ፣ የጠላት ወረራን ለመመከት በተደረጉ ተጋድሎዎች ከነበራት አበርክትዎ በተጨማሪ፤ እንግዳን ተቀብሎ በማስተናገድና የአገር ባለቤት በማድረጉ ረገድ ዓለም በኩራት የሚጻፍላት ክቡድ ታሪኳ ነው፡፡ በአፍሪቃም የሚተካከላት ጥንታዊ ተቋም አለመኖሩን ልብ ይሏል።

ይች የባህል አዋሃጇ እናት ቤተ-ክርስቲያን፡- በአህጉሪቱ ብቸኛ የሆነውን የሳባ ፊደል በመጠቀም፣ ግዕዝን የመንፈሳዊ አገልግሎቷ ቋንቋ በማድረግ፣ የጽሕፈት ባህልን በማዳበር፣ የራስ መለዮን እና የወል-ማንነትን በመቅረጽ አቻ-የለሽ ናት፡፡

በሥነ-መለኮት እና በዓለማዊ ዕውቀት የተራቀቁ ፓትርያርኮችን፣ ሊቃነ-ጳጳሳትን፣ ኤጲስ-ቆጶሳትን፣ ካህናትን፣ ሰባኪያንን፣ ዲያቆናትን፣ መምህራንን… የቀለም ቀንድ አድርጋለች። በአብነት ትምህርት የተጓዘችበት ርቀት ደግሞ፣ እጅግ ዘግይተን በ1900 ዓ.ም በዳግማዊ ዐፄ ምንሊክ በኩል የተዋወቅነው ዘመናዊ ትምህርት በቀላሉ መሬት እንዲረግጥ የነበራት አበርክቶዋ በአገር ባለውለታነት ያስጠራታል፡፡

እስከ 1935 ዓ.ም ድረስ ትምህርት ሚንስቴር ሆና፣ ከሁሉም እምነት ተከታዮች የወጡ ተማሪዎችን በአስኳላው ገርታለች፡፡ ማተሚያ ቤቶች ባልነበሩበት እልፍ ዐመታትም፣ አያሌ መነኮሳት መጽሐፍትን በራሳቸው መንገድ አባዝተው አሰራጭተዋል። ታሪካዊ ሰነዶችን፣ መንፈሳዊና ዓለማዊ መዛግብትን ሰንደው ዘመናትን አሻግረዋል። የኢትዮጵያን ብዝሃ-ታሪክ እና ቅርስን በማስፋፋቱ ረገድም ብሔራዊ ተቋም ነበረች፡፡

በረዥሙ ታሪኳም፣ ገዥዎች በተቀያየሩ እና የሕዝብ እንቅስቃሴዎች ገፍተው በመጡ ቁጥር የተፈራረቁ ፈተናዎችን ተቋቁማ፣ በካህናቶቿ ሐዋርያዊ ትጋት ክርስትናን በአራቱም ማዕዘናት በማስፋፋት የአገር ህላዊ አስቀጣይ ሆና ዘመናትን ዘልቃ፣ ለዛሬ ደርሳለች፡፡

ይህም ሆኖ፣ በውስጣዊም ሆነ በውጫዊ ጥንካሬና ድክመቶቿ የራሷን ወርቃማም ሆነ የጨለማ ዘመናት ማሳለፏ ባይካድም፤ በዚህ ልክ ለሁለንተናዊ ጥቃት ተጋላጭ መሆን ከጀመረች ግማሽ ክፍለ ዘመን እያካለለች ነው፡፡

ከአምስት ዐመቱ የጣሊያን ወረራ በኋላም የለጠቀው ፈተናዋ፣ በአገር በቀል ፋሽስቶች ተደግሞባታልና። የደርግ የዐሥራ ሰባት ዐመታት ፀረ-ሃይማኖት ፖለቲካዊ አስተዳደር ፈተናዎች ሳይዘነጉ፤ ቀኖናዊ ሥርዐቷን በሚጥስ መልኩ የፖለቲካ መዋቅሩ ጣልቃ-ገብነት ማየል የጀመረው ከድኀረ-1983 ወዲህ ነው፡፡

በርግጥም፣ ሕወሓት ለተጠናወተው ከፋፋይ የብሔር ፖለቲካ አደናቃፊነቷን አስልቶ፣ በነፍጥም በፍልጥም ከደርግ እኩል ታግሏታል። በመደብ ጠላትነት ፈርጆም አሳድዷታል። ይህን ተከትሎም፣ ቤተ-ክርስቲያን ፍሬ ነገሯን ለማስቀጠል የህልውና ትግል ላይ ናት፡፡ ኧረ እንዴውም ስደት ላይ ከርማለች።

በተለይ፣ የአስተምህሮት መምታታት እና መንፈሳዊ ተልዕኮን በቅጡ ያለመለየት ችግሮች የውስጣዊ ፈተናዋ አካል ሆነው ጎልተው መውጣታቸው፣ የቤተ-ክርስቲያኗን የህላዌ ትግል ጽኑ አድርጎታል፡፡

ይህ የከረረ የዘውግ-ብሔርተኝነት አራጋቢና ፀረ-ኦርቶዶክስ አገዛዝ፣ ቤተ-ክርስቲያኗን በብርቱ ቢፈትናትም፤ እጅ አለመስጠቷ፣ መከራዋን አክፍቶታል፡፡ በግልባጩ፣ የሀገረ-ስብከት አወቃቀሯ ለዘመናት የተሻገረው መልክዓ-ምድራዊነትና የመንፈሳዊ አገልግሎት አመችነትን ታሳቢ ያደረገ መሆኑ፣ ውስጣዊ አስተዳደሯን በብቸኝነት የምትመራው ቃለ-ዓዋዲን (ሕገ-ቤተ-ክርስቲያንን) መሰረት ያደረገ በመሆኑ፣ ለአክራሪ የዘውግ-ብሔረተኞች እንዳትመች አድርጓታል፡፡ በዚህም ሰርገው በገቡ ኃይሎች እና በተለያየ የፍላጎት ተቃርኖ በቆሙ የውጭ ቡድኖች የማያባራ ጥቃት ሲፈጸምባት ቆይቷል፡፡

ድኀረ-2010 አሕዛቡ ኢሕአዴግ ተነቅሎ፣ አንድ እግሩን ቤተ-መንግሥት ሌላውን ቤተ-እምነት የተከለው እና ፓርቲ ይሁን የሃይማኖት ድርጅት ግራ አጋቢው ‹ብልጽግና› ተተክቷል። ይህንን ተከትሎም፣ በአገሪቷ የፖለቲካ ዐደባባይ የታየው የለውጥ ተስፋ ቤተ-ክርስቲያንንም የጎበኘ ቢሆንም፤ ተስፋዋ ግምጃ በሚቀድ፣ ማቅ በሚያስለብሱ ፈተናዎች የተሞላ ሆኖ ለመታየት ሁለት ክረምት አልወሰደበትም።

በአጭር ጊዜ ውስጥ፣ በአንድ በኩል ኢትዮጵያን ለማፈራረስ፤ በሌላኛው ጫፍ ዐዲስ አገር የመሥራት ፕሮጀክት የያዘ ‹ተረኛ ነኝ› ባይ ኃይል በሁለት ጽንፍ ዒላማ እንዳደረጓት ይፋ ወጥቷልና።

በተለይ፣ ቤተ-ክርስቲያኗ ትኩረቷን የአገር አንድነት ላይ አድርጋ ስትሠራ የኖረች ግዙፍ መንፈሳዊ ተቋም ከመሆኗ አኳያ፣ ዐዲስ አገር የመሥራት ፕሮጀክት ያነገቡ አክራሪ ኃይሎች የጥቃት ሰይፍ መሰንዘራቸው ተገማች ነበር፡፡ ውስጣዊ አንድነቷን በማናጋት የሺሕ ዘመን ታሪኳን ለማውደም የቋመጡ የፖለቲካ ቡድኖች፣ የሃይማኖት ለምድ ለብሰው ከስር-መሰረቷ ሲገዘግዟት ስለመክረማቸውም ከ2010-2015 ዓ.ም ዐቢይ የምስክር ዘመናት ናቸው፡፡

በተለይም፣ ድምፅ-የለሹ የቅባት ኃይል የማንሰራራት ሙከራ (ቤተ-ክርስቲያኗ በአባቶች ብርታት የተሻገረችውን የአስተምህሮ ልዩነት ከተቀበረበት ለመፈልፈል መውተርተሩ) እና ‹‹የኦሮሚያ ቤተ-ክህነት አደራጅ ኮሚቴ›› ተብየው የአንድ ሰሞን ግርግርን ጨምሮ፤ አሁናዊው አቻ ሲኖዶስ ምስረታ... ዐዲስ አገር የማዋለድ ፕሮጀክት ማሳለጫዎች ናቸው።

አንዱ ሲከሽፍ በሁለተኛው፣ ሁለተኛው ሲዘጋ ሦስተኛ ቀውስ እየፈለፈሉ በብዙ ንጠዋታል፡፡ አምስተኛ ረድፉ ጽንፈኛም ከውስጥ ለመሰንጠቅ ሲጋጋጥ፣ ከደጃፏ ያደፈጠው 'የስንዴ ሃይማኖት' መዶሻ እያቀበለ ፈተናዋን አበርትተውታል።

እዚህ ጋ ብዥታ መኖር የሌለበት፣ አፍራሹ ቡድን ቁጥሩ የማይናቅ ቢሆንም፤ መዳረሻቸው ያፈጠጠና ያገጠጠ ኢ-ፍትሐዊነትን በብዙሃን ኢትዮጵያዊ ላይ መጫን ነው፡፡ የሁሉም ቡድኖች አምበል ደግሞ በተረኝነት ስሜት የተወጠረው ኃይል ነው፡፡

ይህ ኃይል፣ "ኢትዮጵያ ሐበሻ-ኦርቶዶክሳዊ ቀለም ያላት አገር በመሆኗ፣ ቀለሟን ለመቀየር  አዕማዷን መናድ ይገባል፤" የሚል ግብ ካስቀመጠ ሰንብቷል። በተሰበረ ልብ ስንታዘባቸው የከረምነው አስጨናቂ ጊዜያቶችም የሚያስረግጡት ይህንኑ ነው።

የኦሮሙማው ቡድኑ ከሱታፌ ይልቅ፣ ሁሉንም የመጠቅለል ሰልቃጭነትን መለያው በማድረጉ፣ ተመክሮም ተዘክሮም የሚድን አይደለም፤ በእጁ የገባውን ሥልጣን ጭምር እንደ አጥፍቶ ጠፊ በራሱ ላይም እየተጠቀመበት ነውና።

@በሙሉዓለም ገ/መድኅን