63 ኢትዮጵያውያንን ያሰረው የታንዛኒያ ፖሊስ አርባዎቹን እያደነ ነው ተባለ
ሐሙስ ሚያዚያ 5 ቀን 2015 (አዲስ ማለዳ) የታንዛኒያ ፖሊስ ሕገወጥ ስደተኞች ናቸው ያላቸውን 63 ኢትዮጵያውያን ያሰረ ሲሆን፤ በሽሽት ላይ ያሉ ቀሪ 40 ስደተኞችን እያደነ መሆኑ ተገልጿል፡፡
ወደ ታንዛኒያ በሕገወጥ መንገድ በመግባት ወደ ደቡብ አፍሪካ ለመሄድ ያቀዱ 100 የሚደርሱ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች በመኪና ተጭነው ሲጓዙ በፖሊስ መያዛቸው ነው የተነገረው፡፡
ስደተኞችን አሳፍሮ ሲጓዝ የነበረው የጭነት መኪና ንጆምቤ በተባለ አውራጃ አደጋ ከደረሰበት በኋላ ለመቆም ቢገደድም 40 ያህል ስደተኞች ማምለጣቸው ተጠቅሷል፡፡
ድካም ውስጥ የነበሩ 63 ስደተኞችን ከእርሻ ቦታዎች ለቃቅሞ ወደ እስር ቤት የወረወረው የታዛንያ ፖሊስ፤ 40ዎችን ለመያዝ እያፈላለገ መሆኑን ዘኢስት አፍሪካ ዘግቧል፡፡
ከምስራቅ አፍሪካ ተነስተው ወደ ደቡብ አፍሪካ ለሚገቡ ሕገወጥ ስደተኞች ታንዛኒያ ቀዳሚ መተላለፊያ መሆኗ ይነገራል፡፡
የኢትዮጵያ ስደተኞችም ከኬንያ ናይሮቢ እና መምባሳ ከተሞች ተነስተው ወደ በሕገወጥ መንገድ ታንዛኒያ የገቡ መሆናቸውን ፖሊስ አረጋግጫለሁ ብሏል፡፡
ደቡብ አፍሪካ፣ ሞዛምቢክ፣ ናሚቢያ እና ቦትስዋና ከምስራቅ አፍሪካ ለሚነሱ ሕገወጥ ስደተኞች የመጨረሻ መዳረሻዎች እንደሆኑም ተጠቁሟል፡፡
በዚህ ወቅት በታንዛኒያ እስር ቤቶች ከ4 ሺሕ 400 በላይ ሕገወጥ ስደተኞች አሉ የተባለ ሲሆን፤ የአገሪቱ መንግሥት በየዓመቱ ከ2 ነጥብ 5 ሚሊዮን ዶላር በላይ ለሆነ ወጭ ይዳረጋል ተብሏል፡፡
አዲስ ማለዳ