Get Mystery Box with random crypto!

† † እንኳን ለቅዱሳት አንስት ሶፍያ ወአዋልዲሃ: ኦርኒ ወማኅበራኒሃ እና ለሊቁ ቅዱስ ጐርጐርዮስ | ✞ገድለ ቅዱሳን✞

† † እንኳን ለቅዱሳት አንስት ሶፍያ ወአዋልዲሃ: ኦርኒ ወማኅበራኒሃ እና ለሊቁ ቅዱስ ጐርጐርዮስ ነባቤ መለኮት ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። † †

† † በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! † †

† † ቅድስት ሶፍያና ልጆቿ † †

† † በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ታዋቂ ከሆኑ የእናቶቻችን ስሞች "ሶፍያ" ቀዳሚው ነው:: ቃሉ በጥሬው ሲተረጐም "ጥበብ (ጥበበ ክርስቶስ) Wisdom of God" ማለት ነው:: ከጻድቃንና ከሰማዕታት ወገን በዚህ ስም የተጠሩ እናቶች አሉ::

ከእነዚህ መካከል አንዷ የሆነችው በዕለቱ የምናስባት እናት ቁጥሯ ከሰማዕታት ነው:: ዋናው ዘመነ ሰማዕታት ከመጀመሩ በፊት የነበረችው ቅድስት ሶፍያ ከሕግ ትዳር 3 ሴቶች ልጆችን አፍርታለች::

ስማቸውንም:- ጲስጢስ (ሃይማኖት) : አላጲስ (ተስፋ) : አጋጲስ (ፍቅር) ስትል ሰይማቸዋለች:: እንደሚገባም በሥርዓቱ አሳድጋ እድሜአቸው 9 : 10 እና 12 ሲደርስ ለሰማያዊ ሙሽርነት አጭታቸዋለች::

በዘመኑ "ክርስቶስን ካዱ" የሚል መሪ ተነስቶ ነበርና ቅዱሳቱ በመድኃኒታችን አምነው : ጣዖትን ዘልፈው አንገታቸውን ሰጥተዋል:: ክብረ ሰማዕትን : ሃገረ ክርስቶስንም ወርሰዋል::

††† ቅድስት ኦርኒ ሰማዕት †††

††† "ኦርኒ" ማለት በምሥራቃውያን ልሳን "ሰላም" ማለት ነው:: ቅድስቲቱ አርበኛ የዘመነ ሐዋርያት የቤተ ክርስቲያን ፍሬ ስትሆን ተወልዳ ያደገችውም በቀድሞው የሮም ግዛት ውስጥ ነው::

ምንም ዛሬ ያለ ትውልድ ቢዘነጋት ቅድስት ኦርኒ ተወዳዳሪ የሌላት ሰማዕት : ሐዋርያዊት : ድንግል ናት:: እርሷ ውበቷን : ንግሥናዋን : ክብሯን : ሃብቷን : ወጣትነቷንና ያላትን ሁሉ ስለ ፍቅረ ክርስቶስ ሰውታለችና ክብርት ናት::

በ1ኛው መቶ ክ/ዘመን መጨረሻ አካባቢ ከሮም ቤተ መንግስት የተወለደችው ቅድስት ኦርኒ እስከ ወጣትነቷ ድረስ ክርስቶስን ልታውቀው አልተቻላትም ነበር:: ምክንያቱ ደግሞ ንጉሡ አባቷ ጣዖትን ማምለኩ ነበር::

ንግሥት እናቷ ምንም ክርስቲያን ብትሆንም ስለ ክርስትና ልትነግራት አልደፈረችም:: ይህን ብታደርግ የሚደርስባትን መከራ ታውቃለችና:: ግን ደግሞ ውስጥ ውስጡን ትጸልይላት ነበርና ፈጣሪ መንገዱን ሊከፍት ጀመረ::

መምለኬ ጣዖት አባቷ ሰው እንዳያያት ቤተ መንግስት ሠርቶ : 12 ሞግዚቶችን መድቦ ጣዖት ከፊቷ አቁሞ ለዘመናት ዘጋት:: የሚገርመው ግን መልኳን እንዳያይ በበር ሆኖ የሚያስተምራት ፈላስፋ ተቀጥሮ ነበርና የዚህ ሰው ማንነቱ ነው::

መምለኬ ክርስቶስ ደግ ሰው ነበርና ፈሊጥን ይሻላት ገባ:: በዚህ መካከል ቅድስት ኦርኒ ራዕይን ታያለች:: የቤቷ መስኮቶች ተከፍተው ሳሉ በስተምሥራቅ ነጭ ርግብ : የዘይት (የወይራ) ዝንጣፊ ይዛ ገብታ : ከማዕዷ ላይ ጥላው ወጣች::

እርሷን ተከትሎ ቁራ በምዕራብ ገባ:: እባቡን ማዕዷ ላይ ጣለው:: በ3ኛው ደግሞ ንስር ገብቶ አክሊል ትቶላት ወጣ:: ቅድስቲቱም እየገረማት አረጋዊ መምህሯን "ተርጉምልኝ" አለችው::

††† እርሱም:-
"•ርግብ=ጥበብ (መንፈስ ቅዱስ)
•ዘይት=ጥምቀት
•ቁራ=ክፉ ንጉሥ
•እባብ=መከራ
•ንስር=ድል ነሺነት (ልዑላዊነት)
•አክሊልም=ክብረ ሰማዕታት ነው" ብሎ ተርጉሞ : ክርስቲያን ሆና ይህ ሁሉ እንደሚደረግ ነግሮ ተሰናበታት::

እርሷም ስትጸልይ ቅዱስ መልአክ ተገልጦ አጽናናት:: ያጠምቃትና ያስተምራት ዘንድም ሐዋርያው ቅዱስ ጢሞቴዎስን ልኮላታል:: ሐዋርያውም የቤተ መንግስቱን ግድግዳ ሰንጥቆ ገብቶ : ለሰማያዊ ሙሽርነት የሚያበቃ ትምህርትና ጥምቀትን ሰጥቷት ሔዷል::

ቅድስት ኦርኒም የአባቷን ጣዖታት ቀጥቅጣ ሰብራ ከአባቷ ጋር ተጣላች:: እርሱም "እገድላታለሁ" ብሎ በእንስሳት ጅራት ላይ ጸጉሯን ሲያስር እንስሶቹ ደንብረው : እጁን ገንጥለው መሬት ላይ ጥለው ገደሉት:: ቅድስት ኦርኒ ግን ጸሎት አድርሳ አባቷን ከሞት አስነሳችው:: እጁንም ቀጠለችለት::

በዚህ ምክንያት በዚያች ዕለት ብቻ አባቷና 30,000 የከተማው አሕዛብ አምነው ተጠምቀዋል:: ቅድስት ኦርኒ ግን ኃይለ መንፈስ ቅዱስ ታጥቃ ክርስትናን ሰበከች:: ብዙም ተሰቃየች:: ንጉሡ ዳኬዎስ : ልጁና ሌሎች 2 ያህል ነገሥታት በእሳት : በአራዊት : በግርፋትና በጦር ፈትነዋታል::

እርሷ ግን ሁሉን በኃይለ ክርስቶስ ድል ነስታለች:: ሙታም የተነሳችበት ጊዜ አለ:: በመጨረሻም በዚህች ቀን ወደ ሰማያዊ ርስት (ገነት) ተመስጣለች:: በዘመነ ስብከቷ ካሳመነቻቸው ባሻገር 130,000 የሚያህሉ ሰዎች ለሰማዕትነት እንዲበቁም ምክንያት ሆናለች::

††† ቅዱስ ጐርጐርዮስ ታኦሎጐስ †††

††† ቅዱሱ:-
•የዘመነ ሊቃውንት ፍሬ:
•የእንዚናዙ ኤጲስ ቆጶስ:
•የቁስጥንጥንያ ፓትርያርክ:
•የጉባዔ ቁስጥንጥንያ (በ381 ዓ/ም) 3ኛ ሊቀ መንበር:
•ባለ ብዙ ድርሳን:
•የቂሣርያ (ቀጰዶቅያ) ኮከብ:
•ብሩህ ገዳማዊ:
•መልካም እረኛ የነበረ አባት ነው::
መጽሐፈ ቅዳሴውን ጨምሮ በጻፋቸው ብዙ መጻሕፍትና በስብከቱ ከሊቃውንት ወገን "ታኦ(ዎ)ሎጐስ" ተብሎ የተጠራ እርሱ ብቻ ነው:: ትርጉሙም በግዕዙ "ነባቤ መለኮት" ማለት ነው:: በአማርኛም "አንድነትን : ሦስትነትን የተናገረ (ያመሠጠረ) እንደ ማለት ነው:: ቅዱሱ ዛሬ ዕረፍቱ ነው::

††† አምላከ ቅዱሳን ከበረከታቸው ይክፈለን፡፡
በመጽናታቸውም ያጽናን፡፡

††† እንዲህ ኃጢአታችን ጽዋዑን ሞልቶ በተረፈበት በዚህ ዘመን አንዲት ሰዓትም ውድ የሆነች የንስሃ ዕድሜ ናት:: እግዚአብሔር ግን ደግ ነውና ይሔው ጥርን አስፈጸመን:: ባይገባን ነው እንጂ በዚሕች ወር ውስጥ ሚሊየኖች በደዌ የአልጋ ቁራኛ ሁነዋል::

ሚሊየኖችም ለንስሃ ሳይበቁ እንዲሁ አንቀላፍተዋል (ሙተዋል):: እስኪ እርሱ አምላካችን ቀሪውን ዘመን ደግሞ ለንስሃና ለመልካም ሥራ ባርኮ ይስጠን::

††† ወርኀ ጥርን በቸር ያስፈፀመ አምላከ ቅዱሳን ወርኀ የካቲትን እንዲባርክልን እንለምነው::

††† ጥር 30 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.ቅድስት ሶፍያና ሦስቱ ሰማዕታት ልጆቿ (ጲስጢስ አላጲስና አጋጲስ)
2.ቅድስት ኦርኒ ሰማዕት ( (በ5 ነገሥታት እጅ የተሰቃየች : የሐዋርያው ጢሞቴዎስ ተከታይና ወደ ብሔረ ሕያዋን የተነጠቀች እናት)
3.ቅዱስ ጐርጐርዮስ ነባቤ መለኮት
4.አባ አክርስጥሮስ
5.አምስቱ ደናግል ሰማዕታት (ጤቅላ: ማርያ: ማርታ: አበያ: ዓመታ)
6.ጻድቃነ ዴጌ (የተሠወሩበት)
7.አባ ሚናስ ሊቀ ጳጳሳት
8."130,000" ሰማዕታት (የቅድስት ኦርኒ ማኅበር)

††† ወርኀዊ በዓላት
1.ቅዱስ ማርቆስ ዘአንበሳ
2.ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቀ መለኮት
3.አባ ሣሉሲ ክቡር

††† "ለእናንተም ጠጉርን በመሸረብና ወርቅን በማንጠልጠል ወይም ልብስን በመጐናጸፍ በውጭ የሆነ ሽልማት አይሁንላችሁ:: ነገር ግን በእግዚአብሔር ፊት ዋጋው እጅግ የከበረ የዋህና ዝግተኛ መንፈስ ያለውን የማይጠፋውን ልብስ ለብሶ የተሰወረ የልብ ሰው ይሁንላችሁ::" †††
(፩ጴጥ. ፫፥፫)

††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††